በወቅቱ የሀገራችን ሁኔታ ሕብረተሰቡን ለከፍተኛ ስጋት የዳረገውን የኮሮና ቫይረስ (COVID-19) ስርጭት ለመግታት ሕብረተሰቡ በየዘርፉ የበኩሉን አስተዋጽኦ እንዲያደርግ ለቀረበው ሀገር አቀፍ ጥሪ የሚድሮክ ቴክኖሎጂ ግሩፕ ማኔጅመንትና ሠራተኞች አፋጣኝ ምላሽ በመስጠት ከፍተኛ አስተዋፅኦ አበረከቱ፡፡ በዚህ ወቅታዊና ዐቢይ ሀገራዊ ጉዳይ መነሻነት የሚድሮክ ቴክኖሎጂ ግሩፕ ማኔጅመንት አመራርና የቴክኖሎጂ ግሩፑ የሠራተኞች ማህበራት የጋራ የምክክር ፎረም አባላት እንዲሁም መላው የኩባንያዎቻችን ሠራተኞች በፈጠሩት የጋራ መግባባትና የዓላማ አንድነት በኩባንያዎቻችን፣ በማኔጅመንት አባላትና በሁሉም ሠራተኞች ስም የብር 10,844,988.91(አሥር ሚሊዮን ስምንት መቶ አርባ አራት ሺህ ዘጠኝ መቶ ሰማንያ ስምንት ብር ከዘጠና አንድ ሳንቲም) ድጋፍ በብሔራዊ ደረጃ ለተቋቋመው የኮሮና ቫይረስ ሚቲጌሽን ትረስት ፈንድ ተበርክቷል፡፡
በዚህም መሰረት የሚድሮክ ቴክኖሎጂ ግሩፕ ቺፍ ኤግዚኪዩቲቭ ኦፊሰርና የዩኒቲ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት አረጋ ይርዳው(ዶ/ር) በዛሬው ዕለት በሰላም ሚኒስቴር የስብሰባ አዳራሽ በተካሔደው ሥነሥርዓት ላይ በመገኘት ይህንኑ ድጋፍ የሚያረጋግጠውን ቼክ ለክቡር አምባሳደር ምስጋናው አረጋ የንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ሚኒስትር ደኤታና የሀብት አሰባሳቢ ንዑስ ኮሚቴ ሰብሳቢ አስረክበዋል፡፡